አንባቢ ያስቀናኛል
ማንበብ ከሚያድለው ብዙ ነገር፣ ከሚያጎናጽፈው እልፍ ክብር እኔን የሚገርመኝ፣ ከአንባቢዎች ጋር ስሆን የሚሰማኝ ስሜት ነው። ስለሆነ ነገር ጨዋታ ሲነሳ፣ ስለአንድ ጉዳይ ማብራሪያ ሲሰጡ፣ ከአፋቸው ማር ጠብ ሲል በጆሮዬ ሳይሆን በነፍሴ አዳምጣቸዋለሁ። አንባቢ ሰዎች በዙሪያዬ ሲኖሩ ማጥራት የፈለኩትን ጉዳይ ሳነሳ በምላሻቸው እደመማለሁ፣ የሃሳባቸው ፍሰት እና ጥንካሬ ከመፅሀፍ ገፅ እየገለጡ የሚያነቡ እንጂ ድንገት የጀመሩት ንግግር አይመስልም። ሰው እንዲህ በእውቀት ይጠቀጠቃል እንዴ ያስብለኛል፣ አለማወቄ የማንበብ ጉጉቴን ይጨምርልኛል፣ አንባቢዎች ሲናገሩ ሰምታችሁ ከሆነ ቃል እና ሃሳብ አይደናቀፉም። ከንግግራቸው ጀርባ ሺህ መፅሀፍት ይታዩኛል። አመክንዮአቸው ያሳምናል፣ መረጋጋታቸው ይማርከኛል። ባጠቃላይ አንባቢዎች ያስቀኑኛል፣ እነሱ በብዙ ድካም አንብበው እንደማር ወለላ ያለቀለትን የነጠረ እውነት ያቀብሉኛል። ጨለማዬን ያበሩልኛል፣ የመረጃ እጥረትን፣ የመረዳት ውስንነትና ክፍተቴን ይሞሉልኛል፣ የዕውቀት ብርሀን ይፈነጥቁልኛል፣ ከጥራዝነጠቅነት ይታደጉኛል። እናም ማንበብን እንድወደው፣ ለማወቅ እንድጓጓ ያደርጉኛልና አንባቢዎች ይብዙልን።
ኢዮብ ጽጌ
ነሀሴ 4, 2016
Responses